Psalms 58

የምድር ዳኞች ፈራጅ

ለመዘምራን አለቃ፤ “አታጥፋ” በሚለው ቅኝት የሚዘመር፤ የዳዊት ቅኔ
ርእሱ የሥነ ጽሑፉን ቅርጽ ወይም የመዝሙሩን ሁኔታ የሚያሳይ ሊሆን ይችላል።

1ኀያላን ሆይ፤ በውኑ ጽድቅ ከአፋችሁ ይወጣል?
የሰው ልጆች ሆይ፤ በቅን ትፈርዳላችሁን?
2የለም፤ በልባችሁ ክፋትን ታውጠነጥናላችሁ፤
በእጃችሁም ዐመፅን በምድር ላይ ትጐነጕናላችሁ።

3ክፉዎች በማሕፀን ሳሉ ከመንገድ የወጡ ናቸው፤
ሲወለዱ ጀምሮ የተሳሳቱና ውሸታሞች ናቸው።
4መርዛቸው እንደ እባብ መርዝ ነው፤
አልሰማ ብላ ጆሮዋን እንደ ደፈነች እፉኝት ናቸው፤
5ጆሮዋንም የደፈነችው የመተተኛውን
ወይም የጠቢቡን ደጋሚ ቃል ላለመስማት ነው።

6አምላክ ሆይ፤ ጥርሳቸውን በአፋቸው ውስጥ ስበር፤
እግዚአብሔር ሆይ፤ የአንበሶቹን መንጋጋ አወላልቅ!
7ፈጥኖ እንደሚያልፍ ወራጅ ውሃ ይጥፉ፤
ቀስታቸውን ሲስቡ ፍላጻቸው ዱልዱም ይሁን።
8ሲሄድ እንደሚቀልጥ ቀንድ አውጣ ይሁኑ፤
ፀሓይን እንደማያይ ጭንጋፍ ይሁኑ።

9የእሾኽ እሳት ገና ድስታችሁን ሳያሰማው፣
ርጥቡንም ደረቁንም እኩል በዐውሎ ነፋስ ጠራርጎ ይወስዳቸዋል።
በዕብራይስጡ የዚህ ሐረግ ትርጕም በትክክል አይታወቅም።

10ጻድቃን በቀልን ባዩ ጊዜ ደስ ይላቸዋል፤
እግራቸውንም በግፈኞች ደም ይታጠባሉ።
11ሰዎችም፣ “በርግጥ ለጻድቃን ብድራት ተቀምጦላቸዋል፤
በእውነትም በምድር ላይ የሚፈርድ አምላክ አለ” ይላሉ።
Copyright information for AmhNASV